በታቦር ተራራ የኾነች ክብርት መገለጥ


በነገረ ሥጋዌ (በነገረ ድኅነት) ታሪክ እጅግ ቁልፍ ቦታ ያላት እለት ናት እለተ ደብረ ታቦር፡፡ ታቦር በተባለው ተራራ ላይ ነቢየ እግዚአብሔር ልበ አምላክ ዳዊት ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ ወይሴብሑ ለስምከ መዝራእትከ ምስለ ኃይል ብሎ ባናገረው ትንቢት መሠረት የዓለም ቤዛ ኢየሱስ ክርስቶስ ቅድመ ዓለም አኗኗሩ ላይ ፍንጭ ሰጠ፡፡

ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከአምላክ ሰው መኾን በላይ ምንም ተአምር/ምልክት የላትም፡፡ ቃል ሥጋ ኮነ፡፡ ከእግዚአብሔር ልዥ መወለድ የሚበልጥ ሌላ ምልክት እንደሌለም ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ “ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልዥም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች” ብሎ ምልክት ለሚሹ ሰዎች ኹሉ የወልደ እግዚአብሔር በሥጋ መገለጥ የነገረ ድኅነት ኹሉ ዐቢይ ምልክት መኾኑን ይናገራል፡፡

በአጭር ቁመትና በጠባብ ደረት ተወስኖ በመካከላችን ሲገኝ ግን ያዩ ሰዎች ይህን ቅድመ ዓለም የነበረ የአብ አካላዊ ቃሉ የእግዚአብሔር ልዥ ነው ብለው ማመን እጅግ ቸግሯቸው ነበር፡፡ ምክንያቱም ከነሙሉ ግርማ መለኮቱ ከነሞገሱ ባለመገለጡ በበህቅ ልሕቀ - ጥቂት በጥቂት አደገ እንዳለ እንደኛው ኹኖ በትሕትና መገኘቱ ነበር፡፡

ይህ ዓይነት መገለጥ እግዚአብሔር አምላክ በሰው ልዦች ያለን እምነት የሚፈትሽበት አገላለጥ ነው፡፡ እግዚአብሔር በእምነት መንገድ የሚፈልጉትና በእምነት መንገድ የሚያገኙት አምላክ በመኾኑ ልዡ ፍጹም በመካከላችን ቢገኝም ቅሉ ርሱ ነው ብሎ ለመቀበልና በዚህም እምነት መንግሥትን ለመውረስ እንድንችል ከፍተኛ የልብ ቀናነትና ፍቅር፣ እግዚአብሔርን በፍጹም ልብ መሻት ያስፈልገን ነበር፡፡

እግዚአብሔር ኹሌም ለፍጥረቱ የተገለጠ የቅርብ አምላክ ነው እንጂ የተሰወረ የሩቅ አምላክ አይደለም፡፡ በክርስትናችን ውስጥ አምላካችን በብዙኅ ነገርና በብዙኅ መክፈልት ተገልጦ ታውቆናል፡፡ ኹሌም ቢኾን እግዚአብሔር ርሱን ማወቅ እስካንችል ድረስ ስውር አይኾንም፤ በመገለጡ ብርሃንም ደግሞ ከልክ በላይ አያጥለቀልቀንም፡፡ ፍጹም ቢሰወረን በኋላ ለምን ዐውቃችሁ አላመለካችሁኝም ማለት አይችልም ነበር፡፡ ፍጹም በመገለጥ ብርሃን ቢያጥለቀልቀን ደግሞ እንካድህ ብንለው እስኪያቅተን ኹኖ በግድም ጭምር ካለ ነጻ ፈቃዳችን እንድናመልከው እንኾናለን፡፡ በእነዚህ በሁለቱ የእግዚአብሔር ፍትሕን ዐዋቂነት አይታይም፤ እሊህ የእግዚአብሔርን ርትዕ አይወክሉም፡፡ በዚህ ምክንያት የእግዚአብሔር መገለጥ የሰው ልዥ በፍጹም ፍቅርና በልብ መሻት ቢፈልገው ብቻ እንዲያገኘው ኹኖ ነው ማለት ነው፡፡ የሚፈልጉት ብቻ እንዲያገኙት ኹኖ ኹሌም ተገልጧል ነው ነገሩ፡፡

የዛሬዋ እለት ታዲያ በማቴ 17:1-9 እንደምናነበው ጌታችን የምሥጢር ሐዋርያትን ሦስቱን አዕማድ ይዞ ሰው ወደማያዘወትረው ታላቅ ተራራ (ታቦር) ወጥቶ እንደነበር እናያለን፡፡ እሊህ ሐዋርያት ሕዝቡ ጌታችንን የተለያየ እንደሚሉትና እነርሱ ግን ርሱ የሕያው የእግዚአብሔር የባሕርይ ልዡ እንደኾነ እንደሚሉ የነገሩት ናቸው፡፡ በፍጹም እምነት ለሚያውቁት ለነርሱ በእምነታቸው ላይ ጨመረላቸው ማለት የተለየ መገለጥ ተገለጠላቸው፤ ምሥጢር ገለጠላቸው፡፡ አንድ ልዥም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የኾነው ክብሩን አየን እንዳሉ ቅድመ ዓለም ከአብ ጋር ያለውን ባሕርይ አሳያቸው፡፡ ይህ ባሕርይ ግን በሥጋ ያሉቱ ሊመለከቱት ሳይችሉ ፍግም ብለው ወደቁ፡፡ በነፍስ በእቅፉ ያሉቱ ግን ሙሴና ኤልያስ በረድኤት ይነጋገሩት ኹሉ ነበር፡፡

የናዝሬቱ ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልዡ ነው፡፡ ሙሴ “በመዠመሪያ ሰማይንና ምድርን ፈጠረ” ብሎ የመሰከረለት ርሱው ነው፡፡ እስራኤልን በቀኙ እየመራ ወደአርነት የወሰዳቸው፤ የተቀደሰ ሕዝብ የካህናት መንግሥት ያደረጋቸው፤ በጠላቶቻቸው ኹሉ ላይ ኃይል እየሰጠ ያኖራቸው ርሱ ነው፡፡ ኋላም ትውልድን ኹሉ ርስት አድርጎ ለአባቱ ሊያገባ፤ የተጨነቁትን በለምለም መስክ ሊያሳርፍ የመጣው ርሱ ነው፡፡

ሠው ኾነ እንጂ ፍጹም አምላክ ነው፤ ተራበ እንጂ ከባለጠግነቱ ርሁባንን የሚቀልባቸው ርሱ ነው፤ ተጠማ እንጂ የሕይወት መጠጥ ነው፤ በማኅፀን ተወሰነ እንጂ ሰማይ ዙፋኑ ምድርም የእግሩ መረገጫ ነች፤ ተያዘ እንጂ ፍጥረትን ኹሉ አጋጥሞ የያዘ ነው፤ ተሰደበ እንጂ በመላእክት ስሙ ሳይቀደስ ለአፍታ እንኳ አይቀርም፤ ተተፋበት እንጂ አእላፍ መናፍስት የባሕርዩን እሳት ያመልጡ ዘንድ ክንፋቸውን የሚጋርዱለት ነው፤ ተቸነከረ እንጂ ዘባነ ኪሩብ እንኳ ዙፋኑን የማይችልለት ንጉሥ ነው፡፡ ይፈርድበት ዘንድ ምድራዊ መሥፍን ፊት አቆሙት እንጂ በትንሣኤ ዘጉባኤ ነፍስ ባለው ኹሉ ላይ ሊፈርድ በዙፋን የሚቀመጠው ርሱ ነው፡፡

የናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ርሱም ሕይወትና መንገድ እውነትም ነው፡፡

መንግሥቱም ቀርባለችና ንስሐ ግቡ!!!

ኃጢአትን ተዉ - ከፍርዱ እንድትድኑ!!!

ሐሰትን ጥሉ፤ በእውነት ላይ አታምጹ፤

አስተያየቶች