ውዳሴ(ከንቱ)

እንደምን አላችሁ! የውዳሴ ኹሉ ባለቤት አባታችን እግዚአብሔር ይመስገን፤አሜን!

እስኪ ዛሬ ደግሞ ለክርስቲያኖች ከዚኽስ የሚበልጥ ጠላት በዓለም ሳሉ የላቸውም  ስለተባለለት ስለ ውዳሴ (ከንቱ) እንምከር፡፡ ታዲያ እርሱን የምንጥልበትን ኹነኛ ስልት ፈልገን እንመክራለን እንጂ ውዳሴ (ከንቱ) ዝክር/መታሰቢያ እስኪገባው ቁምነገር ኹኖ አይደለም፡፡

ውዳሴ ግዕዝ ኾኖ ቀዳማይ ግሥ ወደሰ - አመሰገነ/አሞገሰ - ቀደሰ ብሎ ቅዳሴ እንደሚል  ጥሬ ዘሩ ምስጋና/ሙገሳ ሊል ውዳሴ ይላል፡፡
መወድስ የሚለው ትራስ/መስምም እዚሁ ርባ ግስ ውስጥ ነው፡፡

አንድ ገዳማዊ አባትነበር፡፡ በጾም፣በጸሎት፣በትጋህና በተሀርሞ የሚኖር ብርቱ መንፈሳዊ፡፡ ታዲያ ዲያብሎስ በትሩፋት ተዋግቶ ተዋግቶ ቢያቅተውጊዜ በውዳሴ (ከንቱ) ሊጥለው ማሴር ጀመረ፡፡ ያን ጊዜ ወደአባታችን ተጠግቶ … አንተ አቃትኸኝ አይደል! … ይለዋል፡፡ አዎን አቃትኹህ ቢል በውዳሴ ወድቆ ትሩፋቱ ኹሉ እንደሚመክን ተገንዝቦአባታችን … እኔ ምን አቅትሃለሁ ጌታዬ አቃተህ እንጂ … አለው፡፡ዲያብሎስ ተበሳጭቶ እንዳበደ ውሻ እየተክለፈለፈ ራቀ፡፡ በሕይወት ዘመኑም ኹሉ እየተመላለሰ … አንተ አቃትኸኝ አይደል … ይለው ነበር፡፡ አባታችን ግን ኹሌም … እኔ እንደየት፤ጌታዬን አልቻልኸውም እንጂ! … ይለው ነበር፡፡ ታዲያ የአባታችን ዐረፍተ ሞቱ ደረሰና ነፍሱከሥጋው ተለይታ ወደአጸደ ገነት ስታርግ ዲያብሎስ አሁንም እየተከተለ … አንተ አቃትኸኝ አይደል … ቢል የአባታችን አካለ ነፍስም … እኔ እንደየት፤ጌታዬ አቃተህ … እያለች ትመልሳለች፡፡ በመጨረሻ እገነት በር ደርሳ ልትገባ ጥቂት ሲቀራትዲያብሎስ … አንተ አቃትኸኝ አይደል! ... ሲል ጊዜ ያቺ ነፍስዘወር አለችና በዝግታ ድምፅ … እኔ እንዴት አድርጌ፤ጌታዬን ግን አልቻልኸውም… አለችና በር ተከፍቶላት ገባች፡፡ ያን ጊዜ ዲያብሎስ ከቀደመው ይልቅ በታላቅ ብስጭት በመበሳጨት ያቺን ነፍስ ለአንዴናለመጨረሻ ጊዜ እንዳጣት ዐውቆ ወደተቀረነው ደግሞ መጣ፡፡

ክርስቲያኖች ኹል ጊዜ በትሩፋትና በመልካም ተግባራት ውስጥ መኖር አለባቸው፡፡ ነገር ግን ትሩፋትንና መልካም ምግባርን ማከናወን የመጨረሻው ጽድቅ አይደለም፤እያንዳንዷን በጎ ሥራችንን የሚከተል ግዙፍውጊያ ውዳሴ (ከንቱ) የሚባል አለ፡፡ ይህም ከበጎ ሥራችን በኋላ ከሰዎች ሙገሳንና ዝናን መሻት ነው፡፡ አንዳንዶቻችን ባልሠራነው ሥራ ኹሉ በመጣ ውዳሴ (ከንቱ) እንወድቃለን፡፡ ሰዎች ስለእኛ ያወሯትን ዝና በጥሞና ሰምተን እናጣጥማታለን፤ልባችን ይደሰታል፤አንዳንዴም ደስታችን አምልጦን በፈገግታ ገጻችን ላይ ይገለጣል፡፡ አሊያም ደግሞ ተጨማሪ ውዳሴ በአዲስ መልክ እንዲነገር ሌሎች ወሬዎችን ጨምረን እያወራን እንጋብዛለን፡፡ በሰበብ አስባቡ ሰዎች አይ አንተ! እንዲሉን እንሻለን፡፡ አንተ የሠራኻት ያቺ ሥራኮ ነች ለዚህ ያደረሰችን፤አንተ ከሌለህ አይኾንም፤ወይም አንተ ያለህበት ኹሉ የሠመረ ነው፤አሊያም ደግሞ አንተ የነካኸውን ኹሉ ታሳምራለህ መባልን አብዝተን እንሻለን፡፡ በተግባራችን ኹሉ ከውጤቱ ይልቅ ውዳሴና ዝና የምናመቻች ብዙዎች ነን፡፡ ልምድ በማካፈልና በጎ ተሞክሮ በመግለጥ ሰበብ ንግግራችን ግን ማትረፍ የሚፈልገው በጎ ስምና ዝና ብቻ የሚኾንብን ነን፡፡ ለብዙዎቻችን የንግግራችን መርዘም ምክንያት ነጥብ ለማስያዝ/ቁምነገርን ለመጠቆም ሳይኾን ንግግራችን በጎ ስም የማስገኘት ተጨማሪ ግዳጅ የተሰጠው በመኾኑ ነው፡፡

ውዳሴ (ከንቱ) በሌላ አጠራር “ዜሮ” ብለን ልንጠራው እንችላለን፡፡

ዜሮ በሥነ-ቀመር/ሒሳብ ትምህርት ውስጥ ያለው ድርሻ “ምንም/ባዶ” ነው፡፡ አልፎም ሌሎችን ቁጥሮች እያበዛ ባዶ ያመጣል፡፡ ቁጥሮች ከታናሹ እስከታላቁ በዜሮ ቢባዙ ውጤታቸው ምንም/ባዶ ይሆናል፡፡ውዳሴም የሠራናትን እያንዳንዷን ትሩፋት በዜሮ እያበዛ እንዳልሠራናት የሚያደርግ ነው፡፡ (በሌላ አኳኋን ዜሮ ምንም/ባዶ መሆኑን ትቶ አንደኛውን አሥረኛ፣አሥረኛውን መቶኛ፣መቶኛውን ሺህኛ በማድረግ ቁጥሮችን የሚያበረክትበት አብነት ሲኖር፣ ውዳሴም ቢኾን ከአምላክ ዘንድ ሲሰጥ ስብእናን የሚያከብርበት አብነት አለው፤በቀረው ግን ምሳሌ ዘየኃፅፅ ብለን እናልፋለን፡፡)

ክርስቲያኖች ርስ በርሳችን አንሞጋገስም፤ገጽ በገጽና ቃል በቃል የሚቀርብ ውዳሴ በወንድማችን/እኅታችን ላይ የተሰደደ ቀስት ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች አሉ፤ሰይጣን በውዳሴ (ከንቱ) ሌሎችን ለመጣል ጠንቅ አድርጎ ያበጃቸው፡፡ እኒህ በሰበብ አስባቡ ሰውን ማሞገስ የዘወትር ተግባራቸው የኾነ፣በማሞገስ መልካም ግንኙነት የመሠረቱና ተቀባይነት ያገኙ የሚመስላቸው፡፡ እኒህን ዲያብሎስ አዘጋጃቸው፡፡ ከእነርሱ በሚወጡ የውዳሴ ቃላት ክርስቲያኖችን እየወጋ ይጥላል፤ባሻው ጊዜና ቦታም አፋቸውን አስከፍቶ ይጠቀምባቸዋል፡

ዲያብሎስ ረቂቅ ፍጥረት ነው፡፡ ሥጋና ደም ያልኾነ ብርቱም ነው፡፡ ከሰዎች ይልቅ ጥበበኛና ኹሉን ዐዋቂ፤ሰው ሊያደርግ የማይችለውን የሚችል ነው፤በአጭር አማርኛ በብልጠትና ይኽን በሚመስል ኹሉ እኛን የሰውን ልጆች ይበልጠናል፡፡ ውዳሴ ከተለመዱት ጾሮቹ ኋላ የሚመጣ ጠንካራው ብትሩ ነው፡፡ በሌላ ቢያቅቱኝ በውዳሴ አይችሉኝም ብሎ ይመፃደቃል፡፡(መጽሐፈ ኪዳንን ይመለከቷል፡፡)

በጾም በርትተን፣ለኪዳን ለቅዳሴ ተግተን፣ምጽዋትና ብፅዓቱን አበርክተን አውጥተን፣ሌሎችንም ትሩፋት አድርገንም ቢኾን፤ዲያብሎስ በብልሃት ይኽን በሚመሳስሉ ኹሉ አሁንም ይበልጠናል፡፡ በጾም ጸሎት፣ኪዳንና ቅዳሴ፣ምጽዋትና ብፅዓት ይተወንና ለውዳሴ (ከንቱ) ያቆየናል፡፡ ምናልባት ከኃጢአት ኹሉ የሰው ልጅ በተደጋጋሚ የተፈተነበት ቢኖር ይኸው ነው፡፡

ልንጾም እስከፈቀድነው ድረስ ይተወናል፤ጾምን ስንጨርስ በዚህ ጾር ይፈትነናል፤ጾማችን ለሰዎች እንድትታወቅ እንፈልጋለን፤ጮክ ብለን የምንናገርበትም ጊዜ አለ! ነገር ግን ክርስቲያኖች እናስተውል፤አንዳች በጎ ስምን ሽተን ለሰዎች ትሩፋታችንን ያወጣን ለት ያኔ የደከምንበትን በዜሮ አባዝተን ምንም/ባዶ አምጥተናል፡፡ ዲያብሎስ ያን ጊዜ ዘወር ብሎ በፈገግታ እያላገጠብን ነው፡፡ ምጽዋት አሊያም አንዳች በጎ ምግባር ለሰዎች አድርገን ተመልካች የጠበቅን እንደሁ በዛቹ ቅጽበት የዜሮው ሥነ-ቀመር ውስጥ ገብተናልና አሁንም ሰውየው እየሳቀ ነው፡፡

በነገራችን ላይ የዐዋጅ ጾም የዐዋጅ ስለኾነ ብቻ የጾማችን ሁኔታና ዝርዝር ኹሉ መዘገብ አለበት ማለት አይደለም፡፡ አበው የዐዋጅ ጾም መጽጾሙ በኹሉ ስለሚታወቅ ድብቅ አይደለም ብለው ማስተማራቸው እንደብቅህ ብንለው እንኳ ግልጥ ነው፤መሰወር ይከብዳል ሊሉ እንጂ ለውዳሴና/ለመልካም ስም አሳልፎ የሚሰጥህን ዝርዝር ኹሉ ጨምረህ፣ጥረህ ተጣጥረህ ለሌሎች ግለጠው ማለታቸው አይደለም፡፡ (ፍትኅ መንፈሳዊ በእንተ ጾምን ልብ ይሏል) ስለዚህ በዐዋጅ ምግባራት እንኳ አትርፈን የምንሠራቸው ትሩፋት ኹሉ በልብ የሚቀሩ ናቸው፡፡

ታዲያ ክርስቲያኖች እነዚህን ዐውቀን ብንነቃባቸው እንጠቀማለን፡፡ነገር ግን በዚህ መልኩ ብንረታው እንኳ አሁንም ሰውየው ይበልጠናል፡፡ ይልቁኑ ወደሚብሰው ውዳሴ (ከንቱ) ወስዶ የፈትነናል፡፡ ይኼኔ ውዳሴዋንና ዝናዋን እየሰማናት፤እየተደሰትንባት፣ኧረ እንደውም ተጨማሪ እየፈለግን ነገር ግን ውዳሴ የማንፈልግ አስመስለን ራሳችንን ለሰዎች በማቅረብ፤አዲስ ውዳሴና ዝና እንዲነገርልን ራሳችንን ማሳነስና መውቀስ፣በዚህ ምክንያት የመጣችውን ውዳሴ ግን ልክ እንደቀደመችቱ አጣጥመን በመርካት እንወድቃለን፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ የንግግራችን ቀጥተኛ ዓላማ መፍትኄ በመስጠት አሊያም ነገርን በማጥራት ላይ ያተኩርና ነገር ግን እኛ እንዲገለጥ የምንፈልገው (የጉዳዩ መንትያ ትርጉም) ስለእኛ ሚና የሚጠቁም ይኾንና ሰፋ አድርገን እንናገራለን፤ቃላቱም ኹሉ በዚህ አንፃር ይሰደራሉ፡፡

የሚብስብን ሰዎች ደግሞ ውዳሴ ፈልገን የማያወድሱንን ሰዎች እስከመጥላት እንደርሳለን፡፡ እንዲህ ያለው ሰው የሚነቅፉትን ሰዎች ምን ሊያደርግ እንደሚችል መገመት ይቻላል፡፡ ደግሞ ከዚህም ሲብስ የሚያወድስ ኹሉ ሲጠፋ አፍን አልላቆ ራስን እስከማወደስና ዝናን እስከመንገር የምንደርስ አለን፡፡ ከዚህም መባስ ይችላል፤ያንጊዜ ሌሎች ሰዎች ሲወደሱ ስንሰማ አወዳሹንም ተወዳሹንም እንጠላቸዋለን፤በክስተቱም እንናደዳለን፡፡ እንዲህ ያሉ ሰዎች ሌሎች ሲኮነኑ ደስ ይሰኛሉ፤ምክንያቱም እነርሱ የሚከብሩ ሌሎች ሲዋረዱ ይመስላቸዋልና፡፡

አንድ ሰባኪ ነበር ይላሉ አባቶቻችን የአብነት ቤተ ትምህርት መምህራን፡፡ ስለዝሙት ሲያስተምር የሚያወድሱት፣ስለ ስካር ሲሰብክ ጎሽ የሚሉት መበለት/አሮጊት ነበሩ፡፡ በሌላ ቀን ሰባኪው ስለሐሜት ማስተማር ሲጀምር ጊዜ አሁን አበላሸህ፤እንግዲህ ወሬውን ጀመረው አሉ ይባላል፡፡

ክርስቲያኖች! የሰው ልጅ ምስኪን ፍጥረት ነው፡፡ ንጉሣችን ክርስቶስ እንደየት ሆኖ ከትቢያ እንዳነሣው እናውቃለን፤እውነት ይወራ ከተባለ በመሠረቱ በውዳሴ መፈተን የነበረበት ፍጥረትም አልነበረም፡፡ የሚበላው የሌለው ደኻ ቆሎ እየቆረጠመ የሚያድር ምስኪን በኮሌስትሮል እንደመቸገር ማለት ነው፡፡ ግና ይብዛም ይነስም ውዳሴ (ከንቱ) ኹላችንም አለችብን፡፡ ነገርየው የትኛው ድረስ ከርሯል ነው፡፡

ውዳሴን ከበደሎች ሁሉ የመረረ የሚያደርጉት ሦስት ምክንያቶችአሉ፡፡

አንዱ ከበጎ ተግባር ጋር የተለጠፈና በልብ የሚሠራ ኃጢአት መኾኑነው፡፡ በዚህም አንድ ሰው ልምዱን ማካፈሉና የቀደመ በጎ ተግባሩን መማሪያ አድርጎ ማቅረቡ በጎ ኾኖ ሳለ ከልምድና ተሞክሮ ይልቅ ሚናው ታውቆ እንዲደነቅ ከሻ ልቡ ባለመው መሠረት በደል ይሆንበታል፡፡

ሌላው ውዳሴ መሪር የሚያደርገው የሌሎች ጾሮች/ኃጢአቶች መወለጃ መሆኑ ነው፡፡ ደግን የሚያደርግ ሰው በውዳሴ (ከንቱ) ከተለከፈ ደግነቱን የሚበልጡ ብዙ ኃጢአቶችን ያደርጋል፡፡ በውዳሴ (ከንቱ) የተያዙ ሰዎች ከሚያዘወትሯቸው ኃጢአቶች መሃል ግብዝነት አንዱ ነው፡፡ (ቸርነታቸው በሰው ፊት የተደረገ ወይም ለሰው የተተረከ ነው፡፡ቢያንስ አንድ ሰው የማያውቀው የደግነት ሥራ የላቸውም) ሌሎችም ይሉኝታ ማጣት፣ንዴትና ትእግስት ማጣት፣ሂስና ነቀፋን ለመስማት አቅም ማጣት፣ጥላቻ፣ቅናት፣ፍቅር ማጣት እንዲሁም የእነርሱን ክብር ከፍ ሊያደርጉ የሚችሉ የሚመስሉትን ኹሉ ማድረግ እኒህም እንደ መንቀፍ፣ማዋረድ፣መዋሸት፣ክፋት፣ሴራ፣ደባ የመሳሰሉት ናቸው፡፡ ውዳሴን የሚወድ ሰው ብዙውን ጊዜ ሰዎች በተሰበሰቡበትና በማኅበር ኾነው ባሉበት ቦታ ውስጥ አስቸጋሪ ባሕርያት ይኖሩታል (ነገሩን ኹሉ ለራሱ የሚል ስለኾነ አይስማማም፡፡ ደግሞም ብዙ ሰዎች ጉራንና መኩራራትን ስለሚጠሉ ጭራሽ አይቀበሉትም)፤ተለዋዋጭ እንጂ የተረጋጋ ባሕርይ የሌለው እንደ ኹኔታውና እንደ ክስተቶች የሚኖር ይኾናል (በሚጾሙ ሰዎች ፊት ከምግብ ይታቀባል በሚዝናኑ ሰዎች ፊት ሁሉንም ይበላል)፡፡ የተመረጡና እርሱ የሚከበርባቸው የሚመስለው ቦታዎችንና እኒህ ዓይነት የተወሰኑ ሰዎችን ብቻ ይወዳል፤ያዘወትራል፡፡

የውዳሴ የመጨረሻው ጠንቁ ግን ረድኤተ እግዚአብሔርን ማስረሳቱ ነው፡፡ እግዚአብሔር በዚያ ተግባር ውስጥ የነበረው ድርሻ ሳይኾን ባለቀመሩ ሰው የሠራው ሥራ መጉላቱ እግዚአብሔርን ያስቆጣል፡፡ “እግዚአብሔር ቤትን ካልሠራ ሠራተኞች በከንቱ ይደክማሉ” መዝ. ፻፳፮፥፩ እንዳለ ልበ አምላክ ዳዊት፡፡ ሰውና መላእክት የተፈጠሩ ላንድ ምክንያት ብቻ ነው፤ምስጋናን ለእግዚአብሔር ለመሠዋት፡፡ ታዲያ ሊያመሰግን የተፈጠረ ፍጥረት ምስጋናን ለራሱ ሲያሳድድ ሲኖር የሥነ-ፍጥረቱን ዓላማ ተወ ማለት ነው፡፡ በዚህም ውዳሴ (ከንቱ) ታክሞ መዳን የሚገባው ጽኑ ደዌ ነው፡፡

እንግዲህ ምን እንላለን፤ይኽን ደዌ ቶሎ አክመን ማስወገድ ብቻ አማራጭ ነው፡፡ እንዴት እናክመው፤ በሦስት መንገድ ማከም ይቻላል፤ ራስን/ውስጥን በማየት፣ሌሎችን በማየትና እግዚአብሔርን በማየት፡፡

ራስን ማየት ሲባል በመጀመሪያ ደረጃ ለራሳችን ያለንን አድናቆት ማስወገድ፡፡ “በራስህ አስተያየት ጠቢብ አትሁን” ምሳ. ፫፥፯ እንዳለ፡፡ ሌላው በተደጋጋሚ የተፈተንንበትን ኃጢአት ማሰብ ነው፤ኃጢአቱን የሚያስብ ሰው ሌሎች ሲያወድሱት ስላላወቁ ይላል እንጂ እውነታቸውን አይልም፡፡ ሌላው ያልደረስንባቸውን መዓርጋት ሌሎች ግን የደረሱባቸውን/የሚቀረንን ማሰብ ነው፡፡ በውዳሴ አትሸነፍ ስንል ጭራሽ አትስማው ማለት አይደለም፤ይኽ ከቶ አይቻልም፡፡ ቅሉ ልብህ አታዝልቀው፤አትደሰትበት ማለት ነው፡፡ ከልብህ አንስሥተህ በቃልም ተቃወመው፤አማትብ፤ጌታ ሆይ በዚህች ቅጽበት እየተፈተንኩ ነው፤ድረስልኝ በል፡፡ ያን ጊዜ ምስጋና የባሕርዩ የኾነ ጌታ መጥቶ ያንተን ምስጋና ይወስዳል፤አንተም ትረታለህ፡፡

ሌሎችን ማየት ደግሞ የውስጣችንን ጎዶሎ ካየን በኋላ የሌሎችን በጎና ቀና ነገራቸውን ማየት ነው፡፡ ይኽ ራሳችንን ከእነርሱ እንዳናነፃፅር ወይም እንድናሳንስ ያደርገናል፡፡ሉቃ. ፲፰፥፲፩ ሉቃ.፯፥፵፬‐፵፯ ምንም ቢኾን ባካባቢያችን ያሉትን ሰዎች በዕውቀት ብንበልጣቸው አሊያም በጾም ጸሎት ብንበልጣቸው እነርሱ ደግሞ በትኅትናና ንጹሕ ልቡና፣ራስን በመግዛትና በትዕግሥት ሊበልጡን ይችላሉ፤እግዚአብሔር ደግሞ ይልቁን በእነዚህ ይደሰታል፡፡ ታዲያ ራሳችንን ከሌሎች ማሳነስ ያለብን ወይም የሰዎችን በጎ ነገር ማድነቅ ያለብን ስናወራውና ለሌሎች ስንተርከው ብቻ ሳይኾን ኹል ጊዜም ብቻችንን ኾነን ስናመላልሰውም ነው፡፡

ከኹሉም በላይ ግን ኹል ጊዜ “ያለእኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም”… ዮሐ. ፲፭፥፭ ያለውን አምላክ ማሰብ ነው፡፡ የሠራነውን ኹሉ እርሱ ሠራው፡፡ ውዳሴ በመጣልን ቅጽበት ወደ እርሱ በገጽ ልንመራው ይገባል፡፡ ለትርእይትም ያይደለ ከልብ፡፡ ውዳሴን በመጣበት ቅፅበት በቃል አሰምቶ ተናግሮ መካድ ተገቢ ነው፤ለእግዚአብሔር ማድረግም እንዲሁ፡፡ ከማናቸውም ሥራችን አቅድመን ጊዜ ወስደንና ቦታ ለይተን ጸሎት አድርገን እግዚአብሔርን መለመንም ውጤት ስናገኝ እርሱን እንድናመሰግን ያደርገናል፡፡ የማይጸልይ ሰው ያገኘውን ኹሉ ራሱ ያገኘ ይመስለዋል፡፡ ይኽን ኹሉ አድርገን በውዳሴ ዲያብሎስ ሊረታን ሲያቅተው ደግሞ ያኔም ጥንቃቄ ሊለየን አይገባም፡፡ ምክንያቱም ያኔ ደግሞ በረሳናቸው በቀደሙ ኃጢአቶች ወግቶ ጥሎንም ሊኾን ይችላል፡፡ ለምሳሌ በዝሙት፣በሴሰኝነት፣ገንዘብን በማፍቀርና ሌሎችም፡፡ በኹሉም ቢያቅተው ደግሞ ጠላት ቢያንስ አፋችንን ለውዳሴ በማንሣት በሌሎች ሰዎች ላይ ጠንቅ አድርጎ ያበጀናል፡፡

ነገርየው ከባድ ነው፤ከሕሊናም በላይ፡፡ ደጋግመን በዲያብሎስ ተመትተን ወድቀንም ቢኾን እንኳ አንድ ምትክ የሌለለት ድንቅ መፍትሔ ደግሞ አለ፡፡ ይኽ የነገር ኹሉ ማሰሪያ ሊሆንም ይችላል፡፡“ንስሐ”፡፡

አምላከ አበው ቀደምት፣አምላከ ኩሉ ጥበባት፣አምላከ መላእክት ወኃይላት፣ አጋእዝተ ዓለም ሥላሴ ክብር እስከ ዘለዓለም ይሁንለት፤አሜን!!!

ስብሐት ለእግዚአብሔር ልዑል!!!

አስተያየቶች